የቴፒ ግብርና ምርምር ማዕከል ምርታማነታቸው የተረጋገጠ ከአንድ ሚሊዮን በላይ የቡና ችግኞች ማሰራጨቱን አስታወቀ

የቴፒ ግብርና ምርምር ማዕከል ምርታማነታቸው የተረጋገጠ ከአንድ ሚሊዮን በላይ የቡና ችግኞች ማሰራጨቱን አስታወቀ

የማዕከሉ ዋና ዳይሬክተር ደረጀ ቱሉ(ዶ/ር) እንደገለጹት፤ ማዕከሉ ከተቋቋመበት ዓላማ አንጻር ቴክኖሎጂ በማፍለቅ፣ በማስተዋወቅና በማላመድ ምርታማነታቸው የተረጋገጠ ዘጠኝ የቡና ዝርያዎችን በማሰራጨት ላይ ይገኛል።

ቡና የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ዋልታ እንደመሆኑ ለአካባቢው ሥነ-ምህዳር ምቹ የሆኑ 250 ሺህ ችግኞችን እና 40 ኩንታል የተለያየ ዝርያ ያለው የቡና ዘር ማሰራጨቱን ተናግረዋል።

በአካባቢው ያለውን ከፍተኛ የሕብረተሰብ ፍላጎት ታሳቢ በማድረግ ወጣቶችን፣ ሴቶችንና ሞዴል አርሶ አደሮችን በማደራጀት ስልጠናና ድጋፍ በመስጠት እንዲሁም ምርጥ ዘር በማቅረብ ከ500 ሺህ በላይ ችግኞችን በማሰራጨት ተጠቃሚ እንዲሆኑ መደረጉንም አክለው ገልጸዋል።

በቀጣይም አቅርቦቱን የማሳደግ ሥራ እንደሚሠራና ለደጋማ አየር ንብረት ተስማሚ የሆኑ ዝርያዎችን በምርምር የማስፋፋት ዕቅድ መያዙን ጠቁመዋል።

የቡና ችግኝ ሲወስዱ ያገኘናቸው አቶ ሙሉጌታ ማናዬ በሰጡት አስተያየት፤ በምርምር የተደገፉ ችግኞችን ከዚህ በፊት ወስደው የተከሉ መሆናቸውንና ከሌሎች ችግኞች ጋር ሲነጻጸሩ የተሻለ የዕድገት ደረጃ እንዳላቸው ተናግረዋል።

ሌላኛው ተጠቃሚ አቶ ታረቀኝ ተንኬ በበኩላቸው፤ ሌሎች አርሶ አደሮች ከማዕከሉ ወስደው የተሻለ ተጠቃሚ መሆናቸውን በማየታቸው አሁን ለመትከል ችግኝ መውሰዳቸውን ገልጸው ችግኞችን በስፋት ለመትከል ቢፈልጉም አሁንም የአቅርቦት እጥረት መኖሩን ጠቁመዋል።

ዘጋቢ: በዛብህ ታደሰ – ከማሻ ጣቢያችን