የኢትዮጵያ ፕሪሚዬር ሊግ በሲዳማ ቡና አሸናፊነት ተጠናቀቀ

የኢትዮጵያ ፕሪሚዬር ሊግ በሲዳማ ቡና አሸናፊነት ተጠናቀቀ


የ2018 የውድድር ዘመን ሲቢኢ የኢትዮጵያ ፕሪሚዬር ሊግ በሲዳማ ቡና አሸናፊነት ተጠናቋል።


የውድድር ዓመቱ የመጨረሻ ጨዋታ በሀዋሳ ዩኒቨርስቲ ስታዲየም በሻምፒዮኑ ሲዳማ ቡና እና በኢትዮ ኤሌክትሪክ መካከል ተካሂዷል።


በበርካታ ደጋፊዎች እና የክብር እንግዶች ታጅቦ የተካሄደው የሁለቱ ክለቦች ጨዋታ በኢትዮ ኤሌክትሪክ 1ለ0 አሸናፊነት ተጠናቋል።


ለኢትዮ ኤሌክትሪክ የማሸነፊያ ጎሉን አቤል ሐብታሙ በፍፁም ቅጣት አስቆጥሯል።


ውጤቱን ተከትሎ ሲዳማ ቡና 68 ነጥቦችን ይዞ ሊጉን በቀዳሚነት ሲያጠናቅቅ የውድድር ዓመቱን በድል የቋጨው ኢትዮ ኤሌክትሪክ 5ኛ ደረጃን በመያዝ የውድድር ዓመቱን አጠናቋል።


ሲዳማ ቡና ሻምፒዮን መሆኑን ተከትሎ የኢትዮጵያ ፕሪሚር ሊግ እንደ አዲስ ከተጀመረ በኋላ ዋንጫውን ያሸነፈ 11ኛው ክለብም ሆኗል፡፡


በተጨማሪም ከሀዋሳ ከተማ፣ ከጅማ አባጅፋር፣ መቀሌ 70 እንደርታ እና ፋሲል ከነማ በመቀጠል የፕሪሚዬር ሊጉን ዋንጫ ያነሳ 5ኛው የክልል ክለብም ሆኗል።


በዚህ ዓመት ምድረገነት ሽረ፣ መቀሌ 70 እንደርታ፣ ድሬዳዋ ከተማ እና አርባምንጭ ከተማ ከፕሪሚየር ሊጉ ወደ ከፍተኛ ሊጉ የወረዱ ክለቦች ናቸው።


በአንፃሩ ጋሞ ጬንቻ እና ሀላባ ከተማ ከከፍተኛ ሊጉ ወደ ፕሪሚዬር ሊጉ በማደግ በሚቀጥለው የውድድር በታሪካቸው ለመጀመሪያ ጊዜ በዋናው የሊግ ዕርከን የሚጫወቱ ይሆናል።


ዘጋቢ፡ ሙሉቀን ባሳ