ጥር 29 የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ለመመስረት በሚካሄደው ህዝበ ውሳኔ ድምፃቸዉን ለመስጠት መዘጋጀታቸዉን በጎፋ ዞን የኦይዳ ወረዳ ነዋሪዎች ገለፁ
ጥር 29 አዲሱን የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ለመመስረት የሚያስችለው ህዝበ ውሳኔ በሠላም እንዲጠናቀቅ አስፈላጊው ቅድመ ዝግጅት መደረጉ እና በሁሉም ምርጫ ጣቢያዎች የምርጫ ቁሳቁሶች መድረስ መቻሉን በወረዳዉ ሠላምና ፀጥታ ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ አዳነ እዉነቱ ገልጸዋል።
በወረዳው በ20 ቀበሌያት 26 የምርጫ ጣቢያዎች ያሉ ሲሆን በሁሉም የምርጫ ጣቢያዎች የምርጫ ቁሳቁሶች መድረሳቸው ተገልጿል።
ኃላፊዉ አክለውም የፖሊስ እና የሚሊሻ አባላት በሁሉም ምርጫ ጣቢያዎች መሰማራታቸውን ገልፀዉ ህዝበ ዉሳኔዉ በሠላም እንዲጠናቀቅ ከህብረተሰቡ ጋር በቅንጅት ሊሰራ እንደሚገባ ጠይቀዋል።
በጎፋ ዞን ኦይዳ ወረዳ የግብርና ፅ/ቤት ምክትል ኃላፊና የህዝበ ዉሳኔ አስተባባሪ አቶ ተረፈ ወንድማገኝ ሰኞ ለሚካሄደው የአዲሱ ደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ህዝበ ዉሳኔ ምርጫ የምርጫ ቁሳቁሶች በሁሉም የምርጫ ጣቢያዎች ስርጭት ተጠናቅቋል ብለዋል።
በመጨረሻም ዕድሜያቸው ከ18 ዓመትና ከዚያ በላይ የሆኑና የመራጮች ምዝገባ ካርድ የወሰዱ ዲሞክራሲያዊ መብታቸውን እንዲጠቀሙበት አስተባባሪው ጥሪ አቅርበዋል።
ዘጋቢ: ድሎት ፃፁማ - ከሳውላ ጣቢያችን